ከተሞች የእሳት አደጋን መቆጣጠር በሚያስችል ቁመና ላይ እንደማይገኙ የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ገለጸ፡፡የእሳት አደጋን የመቆጣጠር እና የመከላከል ስራ ትኩረት እንዳልተሰጠው ተነግሯል፡፡ ዘርፉ በሰው ኃይልና በአደረጃጀት እንዳልተጠናከረ የሚናገሩት በከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ማሻሻያ ዳይሬክተር አቶ ተስፋዬ ታረቀኝ ናቸው፡፡
በተለይም ታዳጊ ክልል ከተሞች ላይ መዋቅር ጭምር እንደሌላቸው አቶ ተስፋዬ ያክላሉ፡፡ አደጋው ጊዜ የሚሰጥ ባለመሆኑ ስራው በየከተሞች ተቋማዊ አወቃቀር ሊበጅለት እንደሚገባም ገልጸዋል፡፡በተለያዩ ቦታዎች ያለው አሰራር ባለቤት አልባ መሆኑን ጠቅሰው ለባለሙያዎች ስልጠና ከመስጠት አንስቶ ግብዓቶች እስከማማሏት ያለው ስራ ትኩረት እንዳልተሰጠውም ጠቁመዋል፡፡
አንዳንድ ክልሎች ላይ የሚታየው አሰራር ወጥነት ስለሌለውና አሰራሩ የተቀናጀ ባለመሆኑ አደጋ በሚፈጠርበት ወቅት በቦታው መገኘት የማይቻልበት ሁኔታ መኖሩንም በከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ማሻሻያ ዳይሬክተሩ አቶ ተስፋዬ ታረቀኝ ተናግረዋል፡፡
***************************************************************************
ቀን 19/05/2013
አሐዱ ራዲዮ 94.3