በተያዘው ዓመት ከቤተሰብ የሚለገሰውን የደም አቅርቦት ለማስቀረት እቅድ ተይዞ የነበረ ቢሆንም አሁንም ምቹ ሁኔታዎች ባለመኖራቸው ምክንያት ምትክ ደም ከቤተሰብ እየተወሰደ እንደሚገኝ የብሔራዊ ደም ባንክ ዋና ዳይሬክተር አቶ ያረጋል ባንቴ ለአሐዱ ተናግረዋል፡፡
በዚህም በክልል ደረጃ ትልቁን ድርሻ የሚይዙት በትግራይ ክልል የሚገኙት የአክሱም እና መቀሌ ደም ባንኮች መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ሁመራ የሚገኘው የደም ባንክ እስከ አሁን ወደ አገልግሎት መግባት እንዳልቻለ የተናገሩት አቶ ያረጋል፤ ለማስጀመር የተደረገው ጥረት በተለያዩ ምክንያቶች እየተስተጓጎለ እንደሚገኝ ጠቅሰው ሙሉ ለሙሉ አገልግሎት እየሰጡ እንዳልሆነም ተናግረዋል፡፡
በዓመታዊ የደም አቅርቦት በትግራይ ክልል የሚገኙት የደም ባንኮች ተሳትፎ አመርቂ የነበረ ቢሆንም አሁን ባለው ሁኔታ ግን በአጠቃላይ ለታየው የደም ልገሳ መቀነስ ተጽዕኖ እንደሚኖረው ተናግረዋል፡፡በክልሉ በሆስፒታሎች ለሚሰጡ አገልግሎቶች የደም እጥረት በገጠመበት ወቅት ከቤተሰብ 697 ዩኒት ምትክ የደም አቅርቦት እንደተወሰደ ገልፀዋል፡፡
ቀን 03/10/2013
አሐዱ ራድዮ 94.3