ኢትዮጵያ ከዩክሬን እንቁላል ወደ አገር ውስጥ ለማስገባት በገንዘብ ሚኒስቴር አማካይነት ስምምነት ፈርማለች የተባለዉን መረጃ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ፍጹም ከእዉነት የራቀ ነው ብሎታል፡፡ባለፉት ሁለት ቀናት ኢትዮጵያ ከዩክሬን እንቁላል ወደ አገር ውስጥ ለማስገባት ከአምራቾች ጋር ስምምነት ፈፅማለች የሚል መረጃ በተለያዩ የማህበራዊ ትስስር ገጾች ላይ ሲዘዋወር ቆይቷል፡፡
መረጃዉም ተገኘ የተባለዉ ከዩክሬን ጋዜጦች ላይ ሲሆን አሀዱም የግብርና እና ንግድና ኢንደስትሪ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶችን ጉዳዩ በተመለከተ ጠይቋል፡፡ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶቹም ስምምነት አለመፈጸሙን ለአሀዱ ገልፀዋል፡፡ስምምነቱ ተፈፀመ የተባለው በኢትዮጵያ በኩል ከገንዘብ ሚንስቴር ጋር መሆኑን እና የስምምነቱ ሰነድም ወቷል የሚሉ መረጃዎች እየወጡ መሆናቸዉን ተከትሎ አሀዱም የገንዘብ ሚኒስቴርን ጠይቋል፡፡
የሚንስቴሩ የህዝብ ግንኙነት ዳሬክተር ሳማሪታ ሰዋሰዉ በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በኩል ከዩክሬን እንቁላል ለማስመጣት የተደረገ ስምምነት፤ የተፈረመ ሰነድም የለም ብለዋል፡፡ዳሬክተሯ እንደዚህ አይነት ስምምነቶች ቢኖሩ እንኳን ተጠሪ ተቋማት ሳያዉቁ የሚደረስ ስምምነትም ፊርማም አይኖርም ብለዋል፡፡
ቀን 19/06/2013
አሐዱ ራድዮ 94.3