የካቲት 18/2017 (አሐዱ ሬዲዮ) በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን መርሐቤቴ ወረዳ፣ አገሪት ቁምአንባ ቀበሌ ልዩ ቦታው ቦዳ በተባለ አካባቢ በደረሰ የትራፊክ አደጋ የስድስት ሰዎች ሕይወት አለፈ፡፡

አደጋው የማገዶ እንጨት የጫነ የጭነት ተሽከርካሪ ከላይ 25 ሠራተኞችን አሳፍሮ ሲጓዝ በመገልበጡ መድረሱ ተገልጿል፡፡

በተከሰተው አደጋ የስድስት ሰዎች ሕይወት ማለፉን የወረዳው ፖሊስ ጽ/ቤት የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ሃላፊ ም/ኮማንደር የሺዓለም እንደሻው ተናግረዋል፡፡

በተጨማሪም በ15 ሰዎች ላይ ከባድና ቀላል ጉዳት እንደደረሰ መግለጻቸውን የወረዳው ኮሙኒኬሽን መረጃ ያመላክታል፡፡

የአደጋውን መንስኤ አስመልክቶ መርማሪ ፖሊስ ምርመራውን እያጣራ እንደሚገኝ ተገልጿል።