የካቲት 19/2017 (አሐዱ ሬዲዮ) በአማራ ክልል ለ263 ሺሕ 735 ዜጎች የወሳኝ ኩነት ምዝገባ ማካሄዱን የክልሉ ወሳኝ ኩነት ምዝገባ አገልግሎት አስታውቋል።
አገልግሎቱ የ6 ወራት የእቅድ አፈፃፀም ግምግማን አስመልክቶ፤ ከማእከላዊ፣ ከምዕራብ፣ ከሰሜን ጎንደር ዞኖችና ጎንደር ከተማ አስተዳደር የሚገኙ የዘርፉ ባለሙያዎች፣ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት የተሳተፉበት ውይይት አካሂዷል፡፡
በመድረኩ ላይ የክልሉን የ6 ወራት የእቅድ አፈፃፀም ሪፖርት ያቀረቡት የአገልግሎቱ የእቅድና በጀት ዝግጅት ክትትልና ግምገማ ዳይሮክትሬት ዳይሬክተር አቶ ጥጋቡ ዓለሙ እንደገጹት፤ በበጀት ዓመቱ በክልሉ በሚገኙ 4017 የምዝገባ ጣቢያዎች ለ633 ሺሕ 784 ዜጎች ኩነት ምዝገባ አገልግሎት ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዶ በግማሽ ዓመቱ ለ263 ሺሕ 735 ዜጎች ማከናወን ተችሏል፡፡
ምዝገባ ካካሄዱት መካከል 59 ሺሕ 408 የሚሆኑት በወቅታዊ መዝገባ ያካሄዱ ሲሆን፤ 48 ሺሕ160 በዘገየና ሌሎች ደግሞ በጊዜ ገደቡ ባለፈበት የተመዘገቡ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
ለ263 ሺሕ 735 የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች የምስክር ወረቀት ለመስጠት ታቅዶ፤ 260 ሺሕ 862 ዜጎች መስጠት መቻሉንም ገልጸዋል።
በውይይቱ ማጠቃለያ ላይ የተገኙት የአገልግሎቱ ምክትል ኃላፊ አቶ ሞላ ትዕዛዙ በበኩላቸው፤ "የተቋሙን ደንበኞች ፍላጎት ለማርካት በትኩረት መስራት ይገባል" ብለዋል፡፡
አክለውም በተቋሙ ሊከሰቱ የሚችሉ የብልሹ አሰራር ምልክቶችን መከላከል እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
#አሐዱ_የኢትዮጵያውያን_ድምጽ
በአማራ ክልል ለ263 ሺሕ 735 ዜጎች የወሳኝ ኩነት ምዝገባ መካሄዱ ተገለጸ
