ጥር 5/2017 (አሐዱ ሬዲዮ) በመቀሌ ከተማ ሮማናት አደባባይ በተካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ ላይ፤ 'ይኣክል' ወይንም 'ይበቃል' የሚሉ መፈክሮችን የያዙ በርካታ ሺሕ ሰላማዊ ሰልፈኞች ጥያቄያቸውን ለፕሪቶሪያው ውል ተዋዋዮች አንስተዋል፡፡
ሰላማዊ ሰልፉን ያዘጋጀው "ፅላል ሲቪል ማህበረሰብ ምዕራብ ትግራይ" በሰለፉ ላይ፤ ከ1 ሺሕ 500 እስከ 2 ሺሕ የሚገመት ሕዝብ መሳተፉን ለአሐዱ ገልጿል፡፡
ለአሐዱ ሀሳባቸውን የሰጡት ፅላል አባልና የ'ይአክል' ወይንም 'ይበቃል' ንቅናቄ አስተባባሪ ዳንኤል ነጋሽ፤ የፕሪቶሪያው ሰላም ስምምነት ሙሉ ለሙሉ እንዲከበር የሚጠይቅ ሰልፍ ማድረጋቸውን ተናግረዋል፡፡
የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት ለራሱ ዓላማ ለመጠቀም የሚያስብ አካላቶች እጅ በመውደቁ ከነሱ በማውጣት ለሕዝቡ ጥቅም ላይ እንዲውል አስበው መካሄዱን ተናግረዋል፡፡ አካላት ያሏቸውን ግን ማን እንደሆኑ ከመናገር ተቆጥበዋል፡፡
አቶ ዳንኤል በዛሬው ዕለት የተካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ በዋነኝነት ከምዕራብ ትግራይ ተፈናቅለው በአቢ አዲ እና በሌሎች መጠለያ ካምፖች የሚገኙ ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው እንዲመለሱ የሚጠይቅ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የሰላማዊ ሰልፈኞች ጥያቄ በዋናነት ለተደራዳሪ ወገኖች መሆናቸውን የሚያነሱት አቶ ዳንኤል፤ ጥያቄው በዋናነት ለፌደራል መንግሥት እና ለህወሓት ድርጅት እንዲሁም ይህንን ለማስፈፀም ለተቋቋመው ግዚያዊ አስተዳዳር መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በሰልፉ ላይ 'ይበቃል' የሚል ባነር የያዙ እንዲሁም፤ 'ለ1523 ቀናት በፕላስቲክ ቤት መኖር ይብቃን'፣ 'ጦርነት እንጠየፋለን፤ ሰላም እንሻለን'፣ 'ወደ ቀያችን እንመለስ'፣ 'የፖሪቶሪያው የሰላም ስምምነት ይከበር' እና ሌሎች ጥያቄዎች ተነስተዋል፡፡
ፅላል ሲቪል ማህበረሰብ ምዕራብ ትግራይ በቀጣይ ቀናትም ሰልፉ እንደሚቀጥል የድርጅቱ አባልና የ'ይአክል' ንቅናቄ አስተባባሪ አቶ ዳንኤል ነጋሽ ለአሐዱ ገልጸዋል፡፡