ጥር 3/2017 (አሐዱ ሬዲዮ) ብሔራዊ ባይቶና አባይ ትግራይ፣ አረና ለዲሞክራሲ ለልዑዓላዊነት እና ውድብ ናፅነት ትግራይ የተሰኙ ሦስት በትግራይ ክልል የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎች 'ትግራይን የማዳን ቃል-ኪዳን' በሚል ጥምረት መፍጠራቸውን ገልጸዋል፡፡
በአሁን ሰዓት በትግራይ ህልውና ላይ ከፍተኛ የሆኑ አደጋዎች መጋረጡ ለዚህ ጥምረት ምክንት መሆኑን ለአሐዱ የገለጹት፤ የአረና ለዲሞክራሲ ለልዑዓላዊነት ሊቀመንበር አምዶም ገብረስላሴ ናቸው፡፡

ሊቀመንበሩ ለግዜው የፓርቲያቸውን ፕሮግራም ወደ ጎን በመተው በትግራይ ሉዓላዊ ግዛት ማስከበር ላይ፣ ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው የሚመለሱበትን እና ጠንካራ ድጋፍ የሚደረግበትን ሁኔታ ላይ በጥምረት ለመስራት ማሰባቸውንም ተናግረዋል፡፡
በትግራይ ያሉ መሠረታዊ ችግሮችንና በአጠቃላይ በአሁን ሰዓት ትግራይ ያለችበት ሁኔታ አስቸጋሪ በመሆኑ ፓርቲዎች ይህንን አደጋ ለመመከት ጥምረት መፍጠራቸውን ተናግረዋል፡፡
አሐዱም "ለመሆኑ ይህ በፓርቲዎች ተፈጠረው ጥምረት ውህድ ፓርቲ እንዲሆኑ ነው ወይስ በምን ምልኩ በጋራ ለመስራት ነው የታሰበው?" ሲል ጠይቋል፡፡
የአረናው ሊቀመንበር አምዶም ገብረስላሴ ይህንን ሲመልሱ፤ በሦስቱ ፓርቲዎች መካከል የተደረገው ጥምረት መሆኑን በማንሳት ጥምረቱም በትልልቅ እና አንድ በሚያደረጉ አጀንዳዎች ላይ በጋራ ለመስራት ታስቦ የተመሰረተ መሆኑን ለአሐዱ ተናግረዋል፡፡
"የትግራይ ሕዝብ ሳይድን የሚድን ፓርቲ አይኖርም" የሚሉት ደግሞ ባይቶና አባይ ፓርቲ ሊቀመንበር ክብሮም በረኸ ናቸው፡፡

ፓርቲዎቸ ከትንሽ ጉዳይ እስከ ትልቁ ጉዳይ ላይ በጋራ ለመስራት ማሰባቸውን የሚገልጹት ሊቀመንበሩ፤ "በርካታ ልዩነቶች ቢኖሩብንም ለሕዝቡ ይጠቅማል የሚለውን ሁሉንም ነገር እናደርጋለን" ሲሉ ለአሐዱ ተናግረዋል፡፡
አሐዱም "ለመሆኑ ይህ ጥምረት በቀጣይ ለሚመጣው 7ኛ ዙር ሀገራዉ ምርጫ ላይ በጋራ እስከመወዳር ድረስ የሚደርስ ጥምረት ነው ወይ?" ሲል ጠይቋል፡፡
አቶ ክብሮም በምላሻቸውም "ምርጫው ትንሹ ነገር ነው" ያሉ ሲሆን፤ ከምርጫ ጀምሮ ማንኛውም ዓይነት ጉዳይ ላይ ጥምረት ፈጥረው እንደሚሰሩ ተናግረዋል፡፡
በ2015 ዓ.ም ክረመት ወር ላይ 'ሥር ነቀል ለውጥ' በሚል አምስት የሚሆኑ የክልሉ ፓርቲዎች ሰላማዊ ሰልፍ ላመድረግ ጭምር ሞክረው የነበረ ቢሆንም ብዙ ጥፋት ጠፍቶ መክሸፉ ይታወሳል፡፡

ከአሐዱ ጋር ቆይታ ያደረጉት ፓርቲዎችም የጥምረቱ መነሻው ከዛ ጀመረ መሆኑን በመግለጽ፤ በተለይም የፕሪቶሪያው ሰላም ስምምነት እንዲከበር ጥምረቱ ሥራዎችን እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡